የጌታ የመምጫው ጊዜ ቀርቧል

ሌባ ሳይታሰብ በሌሊት እንደሚመጣ ጌታም እንዲሁ በድንገት ይመጣል (2ኛ ጴጥሮስ 3፡19)፡፡ የጌታ የመምጫ ጊዜ ቅርብ እንደሆነ ለምን እናምናለን? በዙሪያህ እየሆነ ያለውን ስትመለከት፤ ምን ያሳስብሀል?

መጽሀፍ ቅዱስ በመጨረሻው ዘመን ምን እንደሚሆን ይነግረናል፡፡ የተነገረውም እያንዳንዱ ነገር እየተፈፀመ ነው፡፡ “በዚያች ወራት ከጥፋት ውኃ በፊት፥ ኖኅ ወደ መርከብ እስከገባበት ቀን ድረስ፥ ሲበሉና ሲጠጡ ሲያገቡና ሲጋቡም እንደ ነበሩ፥ የጥፋት ውኃም መጥቶ ሁሉን እስከ ወሰደ ድረስ እንዳላወቁ፥ የሰው ልጅ መምጣት ደግሞ እንዲሁ ይሆናል” (ማቴዎስ 24፡38-39)፡፡ እግዚአብሔር የመጀመሪያውን ዓለም ሰው ራስ ወዳድና የልቡም ሀሳብ ክፉ ስለነበረ በውሀ አጠፋው፡፡ ዓለም በአመፃ የተሞላች ነበረች፡፡ እነሱም “ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ” (2ኛ ጢሞቴዎስ 3፡4) ነበሩ፡፡ ዛሬም ሰዎች ከመቼውም ይልቅ ተድላን የሚወዱ ሆነዋል፤ ተድላን ለማግኘትም የተቻላቸውን ሁሉ ያደርጋሉ፡፡

ዓለም ያለችበትን ሁኔታ እስኪ እንመልከት፡፡ ክፋት እና ጥላቻ በብዙ ከተሞች ላይ አይሏል፡፡ ደም መፋሰስና ግድያ እለታዊ ክስተቶች ሆነዋል፡፡ ለምን? ሰዎች እግዚአብሔርን ረስተዋል፡፡ ወጣቶች ቀዥቃዦችና ያልተረጋጉ ሆነዋል? እናትና አባት ልጆቻቸው የቅርብ ክትትል በሚያስፈልጋቸው ወቅት ትተዋቸው ከቤት ርቀው ሄደው  ይሰራሉ፡፡ ወደ ጎዳኖች በመውጣት ለብዙ ችግሮች ተጋላጭ ይሆናሉ፡፡ በወጣትነት እድሜያቸው የሚቀጩ ሰዎች ቁጥር ከአመት አመት እየጨመረ መጥቷል፡፡ ወንጀል ከቀላል ደረጃ ወደ አስከፊ ደረጃ ደርሶአል፡፡ ምን ታስባለህ፤ ነገሮች የሚሻሻሉ ይመስልሀል? ለውጥ የሚታይበት ነገር ተመልክተሀል? ይህ ሁኔታ እስከመቼ ይቀጥል ይሆን? እግዚአብሔር ታጋሽ ነው ነገርግን መንፈሱ ሁሌም ከሰው ጋር ሲታገል አይኖርም፡፡ ሰዎች ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት ስለ ስራቸው መልስ የሚሰጡበት የቁርጥ ቀን ይመጣል፡፡  

የዛሬ ጊዜ ክርስቲያንስ እንዴት ነው? ቅድሚያ መስጠት ላለበት ነገር ቅድሚያን የሚሰጥ ነው? ወይስ ዓለማዊ  ነገሮች አጨናግፈውት እውነተኛ ብርሃኑን እንዳያበራ አግደውታል? የምድር ጨው የማዳን ሀይሉን አጥቶ ይሆን? መጽሀፍ ቅዱስ በእናንተ ያለው ብርሃን ጨልሞ ከሆነ ጨለማው እንዴት ከፍቷል ይለናል፡፡ አዎን ሁላችንም ብርሃኑ እንደበዘዘ ማስተዋል እንዳለብን አምናለሁ፤ ነፍሳትም ሁሉ በታላቁ ፈራጅ ፊት ቆመው ስለ ስራቸው ምላሽ የሚሰጡበት ቀን ቅርብ ነው፡፡

መጽሀፍ ቅዱስ በግልጽ እንደሚለን ኢየሱስ ይመጣል፡፡ “ይህንም ከተናገረ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው እርሱም ሲሄድ ወደ ሰማይ ትኵር ብለው ሲመለከቱ ሳሉ፥ እነሆ፥ ነጫጭ ልብስ የለበሱ ሁለት ሰዎች በአጠገባቸው ቆሙ፤ደግሞም የገሊላ ሰዎች ሆይ፥ ወደስማይ እየተመለከታችሁ ስለ ምን ቆማችኋል? ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲሄድ እንዳያችሁት፥ እንዲሁ ይመጣል አሉአቸው” (የሐዋ. ስራ 1፡9-11)፡፡ ወዳጄ ሆይ፤ ይህ ክስተት ሲሆን አያመልጠንም፡፡ አይን ሁሉ ሲመጣ ያዩታል፡፡ ጌታ ይመጣል፤ ሲመጣም “አሕዛብም ሁሉ በፊቱ ይሰበሰባሉ፤ እረኛም በጎቹን ከፍየሎች እንደሚለይ እርስ በርሳቸው ይለያቸዋል” (ማቴዎስ 25፡32)፡፡ የተወሰኑት ከእርሱ ጋር ወደ ክብር ይሄዳሉ ሌሎች ይቀራሉ፡፡ አንተስ አብረህ ወደ ክብር ትሄዳለህ ወይስ ወደ ኋላ ትቀራለህ? መምረጥ አለብህ፡፡

እኛ ሁላችን ሀጢአተኞች ነን

የተሟላ መልዕክት ክፍል የጌታ የመምጫው ጊዜ ቀርቧል

ሁላችንም ሀጢአትን የሚሰራ ተፈጥሮ አለን፤ ለሀጢአት ባሮች ነን፡፡ እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ተፍተናል፡፡ መልካም የሚያደርግ የለም አንድስ አንኳ፡፡ ማንም ከሀጢአት የነፃሁኝ ነኝ ሊል አይችልም፡፡ መዋሸት፣ ማታለልና መስረቅ የሰው ተፈጥሮው ነው፡፡ ከልጅነታችን ትክክል እንዳልሆኑ እያወቅን የምናደርጋቸው ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ወደ አዋቂነት እድሜ መጥተንም እነዛኑ ነገሮች ለማድረግ እንደምንፈልግ አውቀናል፡፡ ሀጢአት ደመዎዝ አለው፡፡ ዋጋውን ሳይቀበል አይቀርም “በገዛ ሥጋው የሚዘራ ከሥጋ መበስበስን ያጭዳልና” (ገላትያ 6፡8)፡፡ ለሀጢአታችን ብዛት የሚገባውን ካሳ መክፈል የምንችልበት አቅም የለንም፤ ሀጢአትም ከቶ ወደ መንግስተ ሰማይ ሊገባ አይችልም፡፡ ስለዚህ ምን ይበጀናል? ንሰሀ ካልገባን  በስተቀር ተስፋ በሌለበት እንቀራለን፡፡  

አንድ ቀን ጌታ የተዘጋጁትን፣ ዳግም የተወለዱትን ከእርሱ ጋር በክብር እንዲሆኑ ሊወስዳቸው ከሰማይ ይወርዳል (1ኛ ተሰሎንቄ 4፡16-17)፡፡ መንግስተ ሰማይ ያማረና አስደሳች ይሆናል፡፡ “ነገር ግን። ዓይን ያላየችው ጆሮም ያልሰማው በሰውም ልብ ያልታሰበው እግዚአብሔር ለሚወዱት ያዘጋጀው” (1ኛ ቆሮንጦስ 2፡9)፡፡ ዝግጁዎች ካልሆንን ወደ ኋላ እንቀራለን፡፡ መጽሀፍ ቅዱስ፣ ከዚያ በኋላ ምድር በታላቅ ትኩሳት ይቀልጣል ይላል፡፡ ይህም እሳት ለዘለአለም እንደሚሆን ይነግረናል “ትላቸው ወደማይሞትበት እሳቱም ወደማይጠፋበት” (ማርቆስ 9፡44)፡፡ በዚያ ለዘለአለም ልቅሶና ጥርስ ማፏጨት ይሆናል፡፡ ወደ ኋላ ለሚቀሩት ስቃይና መከራ ይሆንባቸውል፡፡ “የሥቃያቸውም ጢስ ለዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ይወጣል” (ራዕይ 14፡11) ይህ ምን ማለት እንደሆነ ጠባብ አእምሮአችን ሊረደው አይችልም፡፡ የጠፋ፤ የተጣለ! ወደ ፊት የተሸለ ይሆናል የሚል ተስፈ የለም፡፡

ከሁሉ የሚያስከፋው፤ ከትዕቢት እና ከቸልተኝነት፣ ከተድላ ወዳጅነትና ከሀጢአት የተነሳ የዘላለም ህይወት ስጦታን ልናጣው መቻላችን ነው፡፡ ጥፋቱ የራሳችን እንጂ የማንም አይሆንም፡፡ የእግዚአብሔር ፍቅር  ከዘለአለም ሞት እጣ ፈንታ ሊያስመልጠን የደህንነትን መንገድ ስላዘጋጀልን ሁልጊዜ መዳን እንችል እንደነበረ አውቀን በምርጫችን በገሀነም እንሆናለን፡፡

ከ ዮሀንስ 3፡16-17 ስለ እግዚአብሔር ፍቅር የተሻለ ማብራሪያን ሊሰጥ የሚችል የለም፡፡ “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ፥ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና”፡፡ ኢየሱስ ሁሉንም ሰው ወደ ህይወት ይጠራል፤ “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ።  ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ ከእኔም ተማሩ፥ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና፥ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤ቀንበሬ ልዝብ ሸክሜም ቀሊል ነውና”፡፡

በብሉይ ኪዳን ዘመን ሁሉ የነበሩ ሰዎች የኮርማ፣ የጠቦት፣ የፍየል እና የእርግብን ደም በማፍሰስ ለሀጢአት ስርየት እንዲሆንላቸው መስዕዋት ያቀርቡ ነበር፡፡ ለሀጢአት ስርይትን ለማግኘት ሞትና የደም መፍሰስ ብቸኛው መንገድ እንደሆነ ተገንዝበው ነበር፡፡ ኢሳያስ 53 ስለ ኢየሱስ “ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት፥ በሸላቶቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ፥ እንዲሁ አፉን አልከፈተም” ብሎ ይነግረናል፡፡ አዎን፤ ካለንበት ከጥፋት መንገድ ለመመለስ ኢየሱስን እንደ አዳኛችን አድርገን መቀበል አለብን፡፡ የእርሱ ደም ለኛ ሀጢአት ስርየት ሆነ፤ የሄደበትን መንገድ መከተል አለብን፡፡ “ኢየሱስም። እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም” (ዮሀንስ 14፡6)፡፡ “ወደ እኔም የሚመጣውን ከቶ ወደ ውጭ አላወጣውም” (ዮሀንስ 6፡37)፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ወደ ኢየሱስ ይጠቁመናል፤ የዓለምን ሀጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ ይለዋል፡፡ መጽሀፍ ቅዱስ ኢየሱስ በምድር ላይ እንዴት እንደኖረ፤ ሸክማቸው የከበደባቸውን እንዴት እንዳሳረፈ፣ የታመሙትን እንደፈወሰ እና ለሞቱት ህይወትን እንደ ሰጠ ይነግረናል፡፡ በመጨረሻም በመስቀል ላይ እንደሞተ ሞትን ድል አድርጎ እንደተነሳም ይነግረናል፡፡ እርሲ ፍጹም የደህንነት መንገድ ሆኖልናል፡፡ ታድያ ይህን ታላቅ የደህንነት መንገድ ቸል ብንል ከእግዚአብሔር ቁጣ እንዴት እናመልጣለን?

የክርስቲያን ሀላፊነት

ከጥቂት ጊዜ በኋላ በምድር ላይ ያለን ቆይታ ያበቃል፡፡ ዋናው ጥያቄ፣ ሀላፊነታችንን ተወጥተናል? ለጠፉ ነፍሳት ስለ ክርስቶስ የመመስከር እድሉን አግኝተን ሳናደርገው ስንቀር አጋጣሚው ያልፈናል፡፡ ያቺ ነፍስ ክርስቶስን ሳታውቅ ወደ ዘለአለም ከተሸገረች ግዴታችንን ተወጥተናል ማለት እንችላለን? ለግድ የለሽነታችን ምን ምላሽ እንሰጣለን?

ጌታ በነብዩ ሕዝቅኤል በኩል እንዲህ ይናገራል፤ “እኔ ኃጢአተኛውንበእርግጥ ትሞታለህ ባልሁት ጊዜ፥ አንተም ባታስጠነቅቀው ነፍሱም እንድትድን ከክፉ መንገዱ ይመለስ ዘንድ ለኃጢአተኛው አስጠንቅቀህ ባትነግረው፥ ያ ኃጢአተኛ በኃጢአት ይሞታል፤ ደሙን ግን ከእጅህ እፈልጋለሁ” (ሕዝቅኤል 3፡18)፡፡ በዚህ ምዕራፍ ላይ ያሉትን አራት ተከታታይ ጥቅሶች አንብብ፡፡ እንነዚህ ጥቅሶች ሊያስፈሩንና ያለብንን ትልቅ ሀላፊነት ሊያስገነዝቡን ይገባል፡፡ እኛ ምስክሮቹ ነን፡፡ ለምድራዊ ነገሮች ያለን አመለካከትና ለመንፈሳዊ ነገሮች ያለን ትጋት ሰዎች ስለ ክርስትና በሚኖራቸው አመለካከት ላይ ተጽኖ ያሳድራል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ሀይል ልንሞላ ያስፈልገናል፡፡ ልባችንም በእግዚአብሔር ፍቅር መሞላት አለበት፡፡ እውነተኛ ምስክሮች እንድንሆን ለሚመፉ ነፍሳት ግድ ሊለን ይገባል፡፡ ብዙ ጊዜ ልባችን እንዲነሳሳ ተግተን ከመጸለይ ይልቅ ይህ እስኪሆን ዝም ብለን እንጠብቃለን፡፡ ክርስቲያን ሆይ ዛሬ፤ በፊታችን ላለው ትግል እራሳችንን እንዴት እናበረታታው? ሀላፊነታችንን እንወጣ ይሆን ወይስ የዘላለም ህይወት ስጦታን እናጣዋለን፡፡ ለጌታ ማድረግ ያለብንን አሁን እናድርግ! “ሊመጣ ያለውም ይመጣል አይዘገይምም” (እብራውያን 10፡37)፡፡

ጌታ ሊመጣ ነው፣ ጊዜው መች እንዲሆን ባናውቅም

በእኩለ ሌሊት አሊያም በጠዋት በቀትርም

ምሽትም ላይ ቢሆን፣ ይመጣል ሊወስደን

እንጠብቀው ይሆን፣ ሁሌም ተዘጋጅተን?

ለተጨማሪ መረጃ ያግኙን

በረሪ የውንጌል ጽሑፎችን (ትራክቶችን) ለማዘዝ

የአእምሮ ሰላም በአስጨናቂው ዓለም

Peace

ሰላም፤ ለአገራችን፣ ለቤታችን በተለይም ለልባችንና ለአእምሮአችን ሰላም የት ይገኛል? በሰዎች ዘንድ የሰላም የጥም ጩኸት ለዘመናት ሲያስተጋባ ኖርዋል፤ በተለይም ዓለም ከጊዜ ወደ ጊዜ እንደ አውሎ ንፋስ እየተናወጠችና ለአስደንጋጭ ክስተቶች ተጋላጭ እየሆነች በመጣች ቁጥር የሰላም ጉጉት ጩኸት ጎልቶ ይሰማል፡፡ ያንተስ የልብህ ጥማት ይሄ ነው? አለመርካትና ሁከት በነገሰበት ዓለም ውስጥ ሁሉን የሚያስንቅ ውስጣዊ ፀጥታን ማግኘት ትፈልጋለህ?

ዓለምን ለኑሮ ተስማሚ እና የተሻለች ለማድረግ የታለመ መጨረሻ የሌለው የስልጣኔ ጉዞ ህይወትን የባሰ ውስብስብ እንዲሆን አድርጎታል፡፡ ምንም እንኳን  ሰዎች በብዙ መልኩ ነገሮች ከወላጆቻቸው የተሻሉ ቢሆኑላቸውም እነርሱ ራሳቸው ግን የተሻሉ አይደሉም፡፡ ሰዎች በድካምና በስጋት ወስጥ ናቸው፡፡ ሰዎች ምሪት እና አማካሪ፣ ጥበቃ እና ዋስትና እንደሚያስፈልጋቸው አጠያያቂ አይደለም፡፡ ሁላችንም የአእምሮ ሠላም እንዲኖረን እንፈልጋለን፡፡

የአእምሮ ሰላም እንዴት ያለ ትልቅ ሀብት ነው! ይህን አይነት ሠላም ግጭትና ተስፋ መቁረጥ፣ አመፃና ችግር በበዛበት ዓለም ውስጥ ማግኘት  ይቻል ይሆን?

የተሟላ መልዕክት ክፍል የአእምሮ ሰላም በአስጨናቂው ዓለም

ታላቁ ፍለጋ ቀጥሏል! ብዙዎች ዝናንና ገንዘብ በማካበት፣ በተድላና በስልጣን፣ በትምህርትና በእውቀት ብዛት እና ትዳር በመመስረት ሰላምን ለማግኘት ይሞክራሉ፡፡ አእምሮአቸውን በእውቀት መሙላት እና ሀብት ማካበትን ይፈልጋሉ፤ ነፍሳቸው ግን ባዶ እንደሆነች ትቀራለች፡፡ ሌሎች በአደንዛዥ እፅ እና በአልኮል የህይወትን ገሃድ (እውነታ) ከመጋፈጥ ለመሸሽ ይሞክራሉ ነገር ግን የሚፈልጉትን ሰላም አያገኙትም፡፡ ፍለጋቸው ሁሉ መውጫ ወደሌለው ተስፋ አስቆራጭና ከንቱነት እሽክርክሮሽ ውስጥ ያስገባቸዋል፡፡ በአስጨናቂው ዓለም ውስጥ ብዙዎች አሁንም በባዶነትና በብቸኝነት አእምሮአቸው እየተጨነቀ ይኖራሉ፡፡

ብዙዎች ውጫዊ ከሆነውና ከሚጨበጠው ነገር ሰላምን ለማግኘት ይጣጣራሉ፤ ወደ ውስጣቸው መመልከትን ግን ቸል ብለዋል፡፡ በውስጣቸው ሊገኝ የሚችለውን  ይፈራሉና፡፡ ስለሚጨነቅ አእምሮአቸው አስጨናቂውን ዓለም ይኮንናሉ፡፡ ፈውስ ግን መጀመር ያለበት ከውስጥ ልባቸው ነው፡፡

ሰው በውጥረት ውስጥ

እግዚአብሔር ሰውን ከፈጠረው በኋላ በፍፁም ሰላም፣ ደስታ እና ተድላ መኖር እንዲችል ባማረ የአትክልት ስፍራ አስቀመጠው፡፡ ነገር ግን አዳምና ሄዋን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በተላለፉባት ሰአት ጸጸት ተሰማቸው ፡፡ በፊት የእግዚአብሔርን መገኘት ይናፍቁ ነበር፤ በኋላ ግን በሀፍረት እራሳቸውን ደበቁ፡፡ ያውቁት የነበረው ሰላምና ደስታ በጸጸትና እና በፍራቻ ተተካ፡፡ የዓለም ብሎም የአእምሮ ጭንቀት የጀመረው እዚህ ጋር ነበር፡፡

እንደ አዳምና ሄዋን አንተም ከእግዚአብሔር ሀሳብ ውጪ ስትሆን ህይወትህ በፍራቻና በጭንቀት ይሞላል፡፡ በኑሮህ እርግጠኛ ስላልሆንክባቸው ነገሮች፣ እየተለዋወጠ እና እያከተመለት ባለው ዓለም ላይ አስኩሮትህን ስታደርግ ሀሳብህን የጣልክበት እና የዋስትናህ መሰረት ይናጋል፡፡ ሰላም አይኖርህም ትረበሻለህ፡፡

ኃጢአት ሰውን ከእግዚአብሔር ለይቶታል፡፡”እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን” (ኢሳያስ 53፡6)፡፡ ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል (ሮሜ 3፡23)፡፡ ኃጢአት፣ ፍራቻ፣ ንዴት ራስ ወዳድነት እና ሌሎችም ጫና እያሳደሩበት ጠላት ሆነው ሰውን በሄደበት ሁሉ የሚከተሉት ቀንበር ሆነውበታል፡፡ እነዚህ መሰላቸትንና የአእምሮ ድካምን ያስከትላሉ፡፡

ራስ ወዳድነት ለሰው የመጀመሪያ አለመታዘዝ ስር መሰረት የጣለ ነበር፡፡ አሁንም ሰውን ወደ ተስፋ መቁረጥና ወደ ልብ ስብራት የሚገፋፋ መሰረታዊ ከሆኑ ክፉ ነገሮች አንዱ ነው፡፡ ለፍላጎቶችህና ለምኞቶችህ ራስወዳድ ከሆንክ  ስግብግብ  እና ጭንቀታም ያደርግሀል፡፡ በራስ ወዳድነትህ ብዙ ከቀጠልክ ጭንቀትህም እየጨመረ ይመጣል፡፡

እግዚአብሔርን ያማከለ ህይወት ሰላምን ይሰጣል

ራስህን የህልውናህ ማዕከል አድርገህ ከመመልከት ይልቅ ወደ እግዚአብሔር መለስ ብለህ እርሱን የህይወትህ አላማ ልታደርገው ያስፈልግሀል፡፡ እግዚአብሔር የህይወትህ ገዢ ካልሆነ ለጠባብ አስተሳሰብ፣ በራስ ለማዘን፣ ለፍራቻ እና ለጭንቀት በቀላሉ ተጋላጭ ትሆናለህ፡፡ መሪህ እግዚአብሔር ከሆነ ሕይወትህ በሁሉም አቅጣጫ የተሟላና በኑሮህም ደስተኛ ትሆናለህ፡፡ በእግዚአብሔር የምትመራ ልብ ብቻ በመረጋጋትና በሰላም ትኖራለች፡፡

መዝሙረኛው ዳዊት “ልቤ ጨካኝ ነው፥ አቤቱ፥ ልቤ ጨካኝ ነው፤ እቀኛለሁ፥ እዘምራለሁ” (መዝ. 57፡7) ብሎ ይናገራል፡፡ በሙሉ ልቡ እግዚአብሔርን በመታመኑ በአእምሮ እረፍት ሀሴት ማድረግ ችሏል፡፡ ልባችን በእግዚአብሔር ላይ ከተደገፈ በዙሪያችን አስጨናቂ ነገሮች ቢኖሩም ውስጣችን ግን ሰላም ይሆናል፡፡ “በሁሉ እንገፋለን እንጂ አንጨነቅም፤ እናመነታለን እንጂ ተስፋ አንቆርጥም” (2ቆሮ. 4፡8) እንደሚለው መሆን ይቻላል፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ የሰላም ምንጭ

ኢየሱስ ሰዎችን ሁሉ አላማ ወዳለው እና ማንነትን ወደ ሚለውጥ ህይወት ይጋብዛል፡፡ “እኔን መከተል የሚወድ ቢኖር፥ ራሱን ይካድ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ” (ማቴ. 16፡24)፡፡ “ስለዚህ ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥረት ነው፤ አሮጌው ነገር አልፎአል፤ እነሆ፥ ሁሉም አዲስ ሆኖአል” (2ቆሮ. 5፡17)፡፡ “ወደ እኔ ኑ” የሚለውን የኢየሱስን ጥሪ ትቀበላለህ? በጨለማ ምትክ ብርሀንን፣ በግራመጋባት ፈንታ መታመንን፣ ለታወከ ሰላምን፣ ላዘነ ደስታን፣ ለደከመ እረፍትን፣ተስፋ ለቆረጠ ተስፋን እና ለሞተው ህይወትን መስጠት ይችላል፡፡  

እግዚአብሔር ሰውን ከአምላኳ ጋር መገናኘትን የምትጠማ ሕያው ነፍስ እንዲኖረው አድርጎ ፈጥሮታል፡፡ “ዋላ ወደ ውኃ ምንጭ እንደሚናፍቅ፥ አቤቱ፥ እንዲሁ ነፍሴ ወደ አንተ ትናፍቃለች። ነፍሴ ወደ ሕያው አምላክ ተጠማች፤ መቼ እደርሳለሁ? የአምላክንስ ፊት መቼ አያለሁ?” (መዝ. 42፡1-2)፡፡ ነፍስን ማርካት የሚችል ሕያው እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ይሄን እርግጠኛ መሆን ትችላለህ፤ ከእግዚአብሔር ጋር ካልተስማማህ በቀር መቼም እውነተኛ ሰላም ሊኖርህ አይችልም፡፡

በልባችን ያለው የውጊያ ሜዳ

ነፍሳችን አምላኳን ብትጠማም በሀጢአት የተሞላ ማንነታችን ግን በእግዚአብሔር ላይ ያምፃል፡፡ ከፊል ማንነታችን እግዚአብሔርን ይናፍቃል ከፊሉ ደግሞ ወደ ስጋ ምኞት ይሳባል፡፡ ልባችን የማያቋርጥ ትግል ያለበት የውጊያ ሜዳ ነው፡፡ ይህ ውስጣዊ ትግል ለውጥረትና ጭንቀት ምክኒያት ይሆናል፡፡ ያለ እግዚአብሔር “እንደሚንቀሳቀስ ባሕር ናቸው፤ ጸጥ ይል ዘንድ አይችልምና፥ ውኆቹም ጭቃና ጕድፍ ያወጣሉና ” (ኢሳ. 57፡20) እንደሚለው ነን፡፡

ህይወታችን ማለትም አእምሮአችን፣ አካላችን እና መንፈሳችን በፈጠረንና እና በሚያውቀን በአንዱ በእግዚአብሔር ካልተስተካከለ በስተቀር ዘላቂ ሰላም ሊኖረን አይችልም፡፡ እርሱ የአለማት ጌታ ብቻ ሳይሆን የእኔን እና ያንተን ሕይወት ከጅማሬው እስከ ፍፃሜውም የሚያውቅ ነው፡፡ ስለኛ በማሰብ ወደ አለም መጣ “ብርሃኑም በጨለማና በሞት ጥላ ተቀምጠው ላሉት ያበራል እግሮቻችንንም በሰላም መንገድ ያቀናል” (ሉቃስ 1፡79)፡፡

የሰላም አለቃ የሆነ ኢየሱስ ወደ እሱ እንድትመጣ ይጠይቅሀል “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ ” (ማቴ. 11፡28)፡፡ ወደ እሱ ስትመጣ በሚሰጥህ ነፃነት እረፍትና እፎይታን ታገኛለህ፡፡ ሰላምህ እንደሚፈስ ወንዝ ይሆናል፤ “ሰላምህ እንደ ወንዝ ጽድቅህም እንደ ባሕር ሞገድ በሆነ ነበር፤ ” (ኢሳ. 48፡18)፡፡ ሸክምህን ሁሉ በእርሱ ላይ በማራገፍ ወደ ኢየሱስ ትመጣለህ? “ሰላምን እተውላችኋለሁ፥ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ . . . ልባችሁ አይታወክ አይፍራም” (ዮሐ. 14፡27) ይልሀል፡፡

 

የፍርሀትና የስጋት መድሀኒት እምነት ነው፡፡ ከዘለአለም እስከ ዘለአለም የሚኖር፣ ከቶ የማይለወጥ ወዳጅ፣ ፍቅሩም የማያረጀውን እግዚአብሔርን መታመን እንዴት እረፍት ነው፡፡ ይህ ወዳጅ ሁሌም ያስብልናል፤ ይጠነቀቅልናል፡፡ ስለዚህ ለምን ሀሳብ ይግባን ለምንስ እንጨነቅ? በ 1ኛ ጴጥ. 5፡7 ላይ “እርሱ ስለ እናንተ ያስባልና የሚያስጨንቃችሁን ሁሉ በእርሱ ላይ ጣሉት” የሚለውን መተግበርን ተለማመድ፡፡ ውጊያው ሲጠናቀቅ ሰላም አለ፤ ታዲያ ህይወትህን ለዚህ ጌታ ለምን አትሰጥም? አስታውስ፣ ካመንክ አትጨነቅም፤ ከተጨነክ አታምንም፡፡ “በአንተ ታምናለችና በአንተ ለምትደገፍ ነፍስ ፈጽመህ በሰላም ትጠብቃታለህ ” (ኢሳ. 26፡3)

ቅሬታ ወይም ንዴት የአእምሮህን ሰላም የሚሰርቅ መርዝ ነው፡፡ ወደ ተስፋ መቁረጥና ተስፋን ወደሚያጨልም ግራ መጋባት ይመራል፡፡ የበደሉህን ሰዎች ይቅርታ ለማድረግ ከባድ ሊሆን ይችላል፤ አንተ ይቅር መባል ከፈለክ ግን ይቅረታ ማድረግ ግዴታህ ነው፡፡ “ለሰዎች ግን ኃጢአታቸውን ይቅር ባትሉ፥ አባታችሁም ኃጢአታችሁን ይቅር አይላችሁም” (ማቴ. 6፡15)፡፡ እምነት በልብህ ሲወለድ ፈቃድህን ለአምላክህ ማስገዛት አይከብድህም፡፡ ቂም ከመያዝና ከመበሳጨት ይልቅ ልብህ በፍቅርና በይቅርታ ይሞላል ከዚያ ውስጣዊ እርጋታን ታገኛለህ፡፡ ኢየሱስ የልብህ ገዢ ሲሆን ጠላቶችህን መውደድ ትችላለህ፡፡ የክርስቶስ ደም ነፃ ሲያወጣህ ብቻ ይህን ማድረግ ትችላለህ፡፡

ሀጢአትን መናዘዝ እና ንሰሀ መግባት የአእምሮ ሠላም ይሰጣል

ከዚህ በፊት የሰራሀቸው የሀጢአቶችህ ሸክም ከብዶህ መሸከም ከምትችለው በላይ እንደሆነ ተሰምቶህ ይሆናል፡፡ ጌታ ለከበደብህ ሸክም በ የሐዋ. ሥራ 3፡19 መፍትሄን ይሰጥሀል፡፡ “እንግዲህ ኃጢአታችሁ እንዲደመሰስ ንስሐ ግቡ፤ ከመንገዳችሁም ተመለሱ፤ በጌታም ዘንድ የመታደስ ዘመን ይመጣላችኋል(አ.መ.ት)”፡፡ (1ዮሐ. 1፡9) “በኃጢአታችን ብንናዘዝ ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዓመፃም ሁሉ ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው” ይላል፡፡ “እንግዲህ በእምነት ከጸደቅን በእግዚአብሔር ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምን እንያዝ” (ሮሜ 5፡1)፡፡

በመዝሙር 23 ላይ ዳዊት በእግዚያብሔር ላይ ያለውን እምነት ይገልፃል፡፡ በህይወቱ ስለተለማመደው ሰላም ሰፊ ማብራሪያ ይሰጣል፡፡ ሰላምና ህብረት ከእረኛው ጋር የጠበቀ ወዳጅነት ላላቸው ሁሉ ነው፡፡

መዝሙር ሀያ ሶስት

እግዚአብሔር እረኛዬ ነው፥ የሚያሳጣኝም የለም።  በለመለመ መስክ ያሳድረኛል፤ በዕረፍት ውኃ ዘንድ ይመራኛል።  ነፍሴን መለሳት፥ ስለ ስሙም በጽድቅ መንገድ መራኝ። በሞት ጥላ መካከል እንኳ ብሄድ አንተ ከእኔ ጋር ነህና ክፉን አልፈራም፤ በትርህና ምርኵዝህ እነርሱ ያጸናኑኛል።  በፊቴ ገበታን አዘጋጀህልኝ በጠላቶቼ ፊት ለፊት ራሴን በዘይት ቀባህ፥ ጽዋዬም የተረፈ ነው። ቸርነትህና ምሕረትህ በሕይወቴ ዘመን ሁሉ ይከተሉኛል፥ በእግዚአሔርም ቤት ለዘላለም እኖራለሁ።

ይሄን እረኛ ታውቀዋለህ? በእርሱ አምነሀል፣ ተደግፈሀል? ኢሳያስ ይህ ሩሩህ እና መሀሪ እረኛ “መንጋውን እንደ እረኛ ያሰማራል፥ ጠቦቶቹን በክንዱ ሰብስቦ በብብቱ ይሸከማል” (ኢሳ. 40፡11) ይለናል፡፡ ከግራ መጋባት ለመውጣትና ዘላለማዊ እረፍረት ወዳለበት የእግዚአብሔር ክንድ ውስጥ ለመግባት ዝግጁ ነህ፡፡ ይለፈውን የሀጢአተኝነት ህይወትህን፣ እያለፍክበት ያለውን ፈተናህን፣ የወደፊት ስጋትህን እና ሙሉ ማንነትህን ለጌታ አሳልፈህ ልትሰጠው ተዘጋጅተሀል፡፡ ጌታ ምርጫውን ያቀርብልሀል፡፡ መወሰን የአንተ ድርሻ ነው፡፡

ዘላቂ ሠላም

በሙሉ ልብህ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ስትመጣ የአእምሮ ሠላምን ለማግኘት የምታደርገው ፍለጋህ ያበቃል፡፡ እርሱን በማመን ብቻ የሚገኝን ሰላምና እረፍት ይሰጥሀል፡፡ እንደ ገጣሚው ለማለትም ትችላለህ፣

ሠላም በሌነበት፣ ሠላምን አውቃለሁ

ወጀብ ባንሰራራበት እርጋታ ያለበት

ሚስጥራዊ በሆነ ቦታ፣ ፊት ለፊት

ከጌታዬ ጋር ልሆን የምችልበት

ራልፍ ስፓልዲንግ ኩሽማን-

 

በአስጨናቂው ዓለም ሠላም ይኖርሀል! የልብህን በር ለክርስቶስ አሁን ክፈትለት፤ እርሱም አንድ ቀን ለዘላለም ፍፁም ዕረፍት ያለበት የመንግስተ ሰማይን በር ይከፍትልሀል፡፡

ለተጨማሪ መረጃ ያግኙን

በረሪ የውንጌል ጽሑፎችን (ትራክቶችን) ለማዘዝ

ንስሐ የምህረት በር

የሰው ልጅ ቅዱስ በሆነው በእግዚአብሔር ፊት በኃጢአቱ ወንጀለኛ ሆኖ በመገኘቱ ሞት እንደተፈረደበት ታውቃለህ? ከዚህ የዘላለም ሞት ፍርድ አምልጦ ለዘላለም ይድን ዘንድ የእግዚአብሔርን ምህረት መቀበል አለበት፡፡ ከዘላለም ሞት አንፃር ምህረት ማለት እግዚአብሔር የሰው ልጅ ሊቀበል ለሚገባው ፍርድ ይቅርታን ሲያደርግ ነው፡፡ ምንም እንኳ ድነት ነጻ የማይከፈልበትና በስራችን የምናገኘው ባይሆንም እግዚአብሔር ግን ምህረቱን ለሰው ልጅ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ አይደለም የሰጠው፡፡ እግዚአብሔር ምህረት የሚደርግበት ቅድመ ሁኔታ ንስሐ ነው፡፡

መጥምቁ ዮሐንስ የእግዚአብሔርን ቃል እየሰበከ ሲመጣ ግልጽና ጠንካራ የነበረው መልዕክቱ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ” (ማቴዎስ 3፥20) የሚል ነበር፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ኢየሱስም አገልግሎቱን የጀመረው “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ” (ማቴዎስ 4፥17) በሚል ተመሳሳይ መልዕክት ነበር፡፡ ሐዋርያው ጴጥሮስ በ(የሐዋርያት ስራ 3፥19) ላይ “ኃጢአታችሁ ይደመሰስ ዘንድ ንስሐ ግቡ ተመለሱም” እንዳለው ለመዳን ንስሐ መግባት አስፈላጊ ነው፡፡ የምህረት በር ተከፍቶ ድነት የሚገኘው በንስሐ አማካኝነት ነው፡፡

ሁሉ ኃጢአትን ሰርተዋል

በዓለማችን ቁጥሩ እጅግ የበዛ ሕዝብ ሲኖር፤ በብዙ መንገዶች አንዳችን ከአንዳችን እንለያያለን፡፡ ነገር ግን “ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል” (ሮሜ 3፥23) የሚለውን መልዕክት ሁላችንም እንጋራዋለን፡፡ ጨምሮም “ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ” (ሮሜ 3፥10) ይላል፡፡ እግዚአብሔር በነብዩ ኢሳይያስ ሲናገር “እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ” (ኢሳይያስ 53፥6) ይላል፡፡ የነዚህን ጥቅሶች ዋና ሐሳብ ልብ ብለሀል? “እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ”፤ “አንድም ጻድቅ የለም”፤ ““ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋል”፡፡ እነዚህ ጥቅሶች አንተን አያካትቱ ይሆን? ነብስህና ሕይወትህ የእግዚአብሔር ነው፡፡ ወንድም ይሁን ሴት ማንም እግዚአብሔርን የሕይወቱ ጌታ አድርጎ የማይቀበል ሁሉ በአመጻና በኃጢአት ይኖራል፡፡ “ኃጢአት የምትሠራ ነፍስ እርስዋ ትሞታለች” (ሕዝቅኤል 18፥4)፡፡

ኃጢአት ያለያያል

ኃጢአትህ ከእግዚአብሔር ጋር አለያይቶሀል፡፡ ልትገልጸው የማትችለው ናፍቆት በውስጥህ ይሰማሀል፡፡ የተረሳህና እግዚአብሔርም የማይሰማ ሊመስልህ ይችላል፡፡ እግዚአብሔር ይህ ለምን እንደሆነ ምክንያቱን እንዲህ ሲል ይነግረናል፡- “እነሆ፥ የእግዚአብሔር እጅ ከማዳን አላጠረችም፥ ጆሮውም ከመስማት አልደነቈረችም ነገር ግን በደላችሁ በእናንተና በአምላካችሁ መካከል ለይታለች፥ እንዳይሰማም ኃጢአታችሁ ፊቱን ከእናንተ ሰውሮታል (ኢሳይያስ 59፥1-2)። ጨምሮም (ሮሜ 6፥23) ላይ “የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነው” ይለናል። ስለ ሕይወትህና ስለ ኃጢአትህ ስታስብ ስለ እግዚአብሔርም አስብ፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ ኃጢአት የለም፡፡ ስለዚህ እርሱ ቅዱስ ጻድቅና የማያዳላ አምላክ ነው፡፡ “እግዚአብሔር ሥራን ሁሉ የተሰወረውንም ነገር ሁሉ፥ መልካምም ቢሆን ክፉም ቢሆን፥ ወደ ፍርድ (በማምጣት)” (መክብብ 12፥14) ለኃጢአት ፍርድ እንደሚገባው ይነግረናል። በአንተና በእግዚአብሔር መካከል ሰፊ መራራቅ ተፈጥሯል፡፡ በቅዱሱ እግዚአብሔር እና በኃጢአተኛው ሰው መካከል የተፈጠረውን መራራቅ የሚያስታርቀውን መንገድ እስካላገኘህ ድረስ የዘላለም ሞትን ትሞታለህ! (ሉቃስ 16፥26)፡፡ ነገር ግን የምስራች፣ መንገድ አለ፣ ተስፋም አለልህ!

የተሟላ መልዕክት ክፍል ንስሐ የምህረት በር

እግዚአብሔር በኃጢአት ላይ የሞትን ፍርድ ያስተላለፈ ቢሆንም፤ “እግዚአብሔር ፍቅር ነው” (1ዮሐንስ 4፥16) እንደሚል እርሱ የፍቅር አምላክ ነው፡፡ በኃጢአት የምትኖር እንኳን ቢሆን እግዚአብሔር ይወድሀል፡፡ ከፍቅሩ የተነሳ ትድን ዘንድ መንገድን አዘጋጅቶልሀል (ዮሐንስ 3፥16)፡፡ እግዚአብሔር በኃጢአት ላይ የፈረደውን ፍርድ ቢፈጽም ሰው በቅጽበት ይሞታል፡፡ ነገር ግን ማንም እንዲይጠፋ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የኃጢአታችንን ቅጣት ተቀብሎልን በሕይወት እንኖር ዘንድ ልጁን ኢየሱስን ልኮልናል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “እንግዲህ የእግዚአብሔርን ቸርነትና ጭከና ተመልከት” (ሮሜ 11፥22)  ይላል፡፡ የእግዚአንሔር ቸርነት ሰው ሁሉ እንዲድን መፈለጉ ሲሆን ፍርዱ ደግሞ መቀጣት ያለበትን ሁሉ ይቀጣል፡፡

ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም የመጣው ነብሳችንን ለማዳን ነው፡፡ እርሱ ምንም ኃጢአት ያልተገኘበት ቅዱስ የእግዚአብሔር በግ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ለኛ ያለው ፍቅር የተረጋገጠው ኃጢአትና በደላችንን ሁሉ ወስዶ በኢየሱስ ላይ ባኖረበት ግዜ ነው፡፡ ቸርነቱን ተመልከት! ኢየሱስ በኛ ቦታ ሆኖ ኃጢአት በመሆን የእግዚአብሔር ፍርድ እንዲፈጸም በመስቀል ላይ ተሰቀለ፡፡ መከራና ስቃይንም ተቀብሎ ሞተ፡፡ የኃጢአታችንም ዋጋ ተከፈለ፡፡ የእግዚአብሔርን ጭካኔ ተመልከት!

ንስሐ፣ የእኛ ድርሻ

ኢየሱስ እንደሞተልህ ትረዳ ይሆን? በኃጢትህ ምክንያት መሞቱንስ ታስተውል ይሆን? ኢየሱስን የሰቀለው ማን ነበር? የአይሁድ መሪዎች፣ ጲላጦስ ወይስ የሮም ወታደሮች ብቻ ይሆኑ ለኢየሱስ መሰቀል ተጠያቂዎች? ሐዋርያው ጴጥሮስ በሺዎች ለሚቆጠሩ ሰዎች ሲሰብክ “……ሰቅላችሁ ገደላችሁት” በማለት ይሰሙት የነበሩት ህዝብ ለኢየሱስ መሰቀል ተጠያቂዎች እንደነበሩ በ(የሐዋርያት ስራ 2፥16) ላይ ሲነግራቸው እናነባለን፡፡ ተሰቅሎ ወደነበረው ኢየሱስ ተመልከትና ለኃጢአተኛነትህ እውቅናን ስጥ፡፡

የጠፋህ መሆንህና እርዳታ እንደሚያስፈልግህ በእግዚአብሔር መንፈስ ኃይል ትረዳለህ፡፡ ይህ መረዳት በልብህ እየጠነከረ ሲመጣ የኃጢአተኝነት ሸክም በርትቶ ስለ ኃጢአትህ መጸጸት እንዲሆንልህ ያደርጋል፡፡ ያን ጊዜም “እኔን ኃጢአተኛውን ማረኝ” (ሉቃስ 18፥13) በማለት ወደ እግዚአብሔር መጮህ ይሆንልሀል፡፡ እግዚአብሔርም ከልብ የሆነ ጩኸትህን ሰምቶ ያድንሀል፡፡ ሸክምህም ሁሉ ተራግፎልህ ዳግም ትወለዳለህ፡፡ ኢየሱስን መከተልህን ስትቀጥል ከኃጢአት መንገዶችህ ሁሉ ፊትህን በማዞር ሰማያዊውን መንገድ ትከተላለህ፡፡ እግዚአብሔር ወደ እርሱ ለሚመጡ ሁሉ በልባቸው የሚሰራው ስራ እና የንስሐ መንገድ ይህን ይመስላል፡፡ ልብህ ታጥቦና ነጽቶ ሰላም ደስታና መተማመን ይሆንልሀል፡፡

በመጨረሻም ንስሐ በክርስቶስንና በእግዚአብሔርን ፍቃድ ደስ እየተሰኘህ አመስጋኝና ታማኝ እንድትሆን ያደርግሀል፡፡ ሞት ተፈርዶብንና መውጫው ጠፍቶን ሳለ ክርስቶስ “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ” (ማቴዎስ 11፥28) አለን። “እርሱ አስቀድሞ ወዶናልና እኛ እንወደዋለን” (1ዮሐንስ 4፥19)፡፡   

ለተጨማሪ መረጃ ያግኙን

በረሪ የውንጌል ጽሑፎችን (ትራክቶችን) ለማዘዝ