ንስሐ የምህረት በር

የሰው ልጅ ቅዱስ በሆነው በእግዚአብሔር ፊት በኃጢአቱ ወንጀለኛ ሆኖ በመገኘቱ ሞት እንደተፈረደበት ታውቃለህ? ከዚህ የዘላለም ሞት ፍርድ አምልጦ ለዘላለም ይድን ዘንድ የእግዚአብሔርን ምህረት መቀበል አለበት፡፡ ከዘላለም ሞት አንፃር ምህረት ማለት እግዚአብሔር የሰው ልጅ ሊቀበል ለሚገባው ፍርድ ይቅርታን ሲያደርግ ነው፡፡ ምንም እንኳ ድነት ነጻ የማይከፈልበትና በስራችን የምናገኘው ባይሆንም እግዚአብሔር ግን ምህረቱን ለሰው ልጅ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ አይደለም የሰጠው፡፡ እግዚአብሔር ምህረት የሚደርግበት ቅድመ ሁኔታ ንስሐ ነው፡፡

መጥምቁ ዮሐንስ የእግዚአብሔርን ቃል እየሰበከ ሲመጣ ግልጽና ጠንካራ የነበረው መልዕክቱ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ” (ማቴዎስ 3፥20) የሚል ነበር፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ኢየሱስም አገልግሎቱን የጀመረው “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ” (ማቴዎስ 4፥17) በሚል ተመሳሳይ መልዕክት ነበር፡፡ ሐዋርያው ጴጥሮስ በ(የሐዋርያት ስራ 3፥19) ላይ “ኃጢአታችሁ ይደመሰስ ዘንድ ንስሐ ግቡ ተመለሱም” እንዳለው ለመዳን ንስሐ መግባት አስፈላጊ ነው፡፡ የምህረት በር ተከፍቶ ድነት የሚገኘው በንስሐ አማካኝነት ነው፡፡

ሁሉ ኃጢአትን ሰርተዋል

በዓለማችን ቁጥሩ እጅግ የበዛ ሕዝብ ሲኖር፤ በብዙ መንገዶች አንዳችን ከአንዳችን እንለያያለን፡፡ ነገር ግን “ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል” (ሮሜ 3፥23) የሚለውን መልዕክት ሁላችንም እንጋራዋለን፡፡ ጨምሮም “ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ” (ሮሜ 3፥10) ይላል፡፡ እግዚአብሔር በነብዩ ኢሳይያስ ሲናገር “እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን ከእኛ እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ” (ኢሳይያስ 53፥6) ይላል፡፡ የነዚህን ጥቅሶች ዋና ሐሳብ ልብ ብለሀል? “እያንዳንዱ ወደ ገዛ መንገዱ አዘነበለ”፤ “አንድም ጻድቅ የለም”፤ ““ሁሉ ኃጢአትን ሠርተዋል”፡፡ እነዚህ ጥቅሶች አንተን አያካትቱ ይሆን? ነብስህና ሕይወትህ የእግዚአብሔር ነው፡፡ ወንድም ይሁን ሴት ማንም እግዚአብሔርን የሕይወቱ ጌታ አድርጎ የማይቀበል ሁሉ በአመጻና በኃጢአት ይኖራል፡፡ “ኃጢአት የምትሠራ ነፍስ እርስዋ ትሞታለች” (ሕዝቅኤል 18፥4)፡፡

ኃጢአት ያለያያል

ኃጢአትህ ከእግዚአብሔር ጋር አለያይቶሀል፡፡ ልትገልጸው የማትችለው ናፍቆት በውስጥህ ይሰማሀል፡፡ የተረሳህና እግዚአብሔርም የማይሰማ ሊመስልህ ይችላል፡፡ እግዚአብሔር ይህ ለምን እንደሆነ ምክንያቱን እንዲህ ሲል ይነግረናል፡- “እነሆ፥ የእግዚአብሔር እጅ ከማዳን አላጠረችም፥ ጆሮውም ከመስማት አልደነቈረችም ነገር ግን በደላችሁ በእናንተና በአምላካችሁ መካከል ለይታለች፥ እንዳይሰማም ኃጢአታችሁ ፊቱን ከእናንተ ሰውሮታል (ኢሳይያስ 59፥1-2)። ጨምሮም (ሮሜ 6፥23) ላይ “የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነው” ይለናል። ስለ ሕይወትህና ስለ ኃጢአትህ ስታስብ ስለ እግዚአብሔርም አስብ፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ ኃጢአት የለም፡፡ ስለዚህ እርሱ ቅዱስ ጻድቅና የማያዳላ አምላክ ነው፡፡ “እግዚአብሔር ሥራን ሁሉ የተሰወረውንም ነገር ሁሉ፥ መልካምም ቢሆን ክፉም ቢሆን፥ ወደ ፍርድ (በማምጣት)” (መክብብ 12፥14) ለኃጢአት ፍርድ እንደሚገባው ይነግረናል። በአንተና በእግዚአብሔር መካከል ሰፊ መራራቅ ተፈጥሯል፡፡ በቅዱሱ እግዚአብሔር እና በኃጢአተኛው ሰው መካከል የተፈጠረውን መራራቅ የሚያስታርቀውን መንገድ እስካላገኘህ ድረስ የዘላለም ሞትን ትሞታለህ! (ሉቃስ 16፥26)፡፡ ነገር ግን የምስራች፣ መንገድ አለ፣ ተስፋም አለልህ!

የተሟላ መልዕክት ክፍል ንስሐ የምህረት በር

እግዚአብሔር በኃጢአት ላይ የሞትን ፍርድ ያስተላለፈ ቢሆንም፤ “እግዚአብሔር ፍቅር ነው” (1ዮሐንስ 4፥16) እንደሚል እርሱ የፍቅር አምላክ ነው፡፡ በኃጢአት የምትኖር እንኳን ቢሆን እግዚአብሔር ይወድሀል፡፡ ከፍቅሩ የተነሳ ትድን ዘንድ መንገድን አዘጋጅቶልሀል (ዮሐንስ 3፥16)፡፡ እግዚአብሔር በኃጢአት ላይ የፈረደውን ፍርድ ቢፈጽም ሰው በቅጽበት ይሞታል፡፡ ነገር ግን ማንም እንዲይጠፋ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የኃጢአታችንን ቅጣት ተቀብሎልን በሕይወት እንኖር ዘንድ ልጁን ኢየሱስን ልኮልናል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “እንግዲህ የእግዚአብሔርን ቸርነትና ጭከና ተመልከት” (ሮሜ 11፥22)  ይላል፡፡ የእግዚአንሔር ቸርነት ሰው ሁሉ እንዲድን መፈለጉ ሲሆን ፍርዱ ደግሞ መቀጣት ያለበትን ሁሉ ይቀጣል፡፡

ኢየሱስ ወደዚህ ዓለም የመጣው ነብሳችንን ለማዳን ነው፡፡ እርሱ ምንም ኃጢአት ያልተገኘበት ቅዱስ የእግዚአብሔር በግ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ለኛ ያለው ፍቅር የተረጋገጠው ኃጢአትና በደላችንን ሁሉ ወስዶ በኢየሱስ ላይ ባኖረበት ግዜ ነው፡፡ ቸርነቱን ተመልከት! ኢየሱስ በኛ ቦታ ሆኖ ኃጢአት በመሆን የእግዚአብሔር ፍርድ እንዲፈጸም በመስቀል ላይ ተሰቀለ፡፡ መከራና ስቃይንም ተቀብሎ ሞተ፡፡ የኃጢአታችንም ዋጋ ተከፈለ፡፡ የእግዚአብሔርን ጭካኔ ተመልከት!

ንስሐ፣ የእኛ ድርሻ

ኢየሱስ እንደሞተልህ ትረዳ ይሆን? በኃጢትህ ምክንያት መሞቱንስ ታስተውል ይሆን? ኢየሱስን የሰቀለው ማን ነበር? የአይሁድ መሪዎች፣ ጲላጦስ ወይስ የሮም ወታደሮች ብቻ ይሆኑ ለኢየሱስ መሰቀል ተጠያቂዎች? ሐዋርያው ጴጥሮስ በሺዎች ለሚቆጠሩ ሰዎች ሲሰብክ “……ሰቅላችሁ ገደላችሁት” በማለት ይሰሙት የነበሩት ህዝብ ለኢየሱስ መሰቀል ተጠያቂዎች እንደነበሩ በ(የሐዋርያት ስራ 2፥16) ላይ ሲነግራቸው እናነባለን፡፡ ተሰቅሎ ወደነበረው ኢየሱስ ተመልከትና ለኃጢአተኛነትህ እውቅናን ስጥ፡፡

የጠፋህ መሆንህና እርዳታ እንደሚያስፈልግህ በእግዚአብሔር መንፈስ ኃይል ትረዳለህ፡፡ ይህ መረዳት በልብህ እየጠነከረ ሲመጣ የኃጢአተኝነት ሸክም በርትቶ ስለ ኃጢአትህ መጸጸት እንዲሆንልህ ያደርጋል፡፡ ያን ጊዜም “እኔን ኃጢአተኛውን ማረኝ” (ሉቃስ 18፥13) በማለት ወደ እግዚአብሔር መጮህ ይሆንልሀል፡፡ እግዚአብሔርም ከልብ የሆነ ጩኸትህን ሰምቶ ያድንሀል፡፡ ሸክምህም ሁሉ ተራግፎልህ ዳግም ትወለዳለህ፡፡ ኢየሱስን መከተልህን ስትቀጥል ከኃጢአት መንገዶችህ ሁሉ ፊትህን በማዞር ሰማያዊውን መንገድ ትከተላለህ፡፡ እግዚአብሔር ወደ እርሱ ለሚመጡ ሁሉ በልባቸው የሚሰራው ስራ እና የንስሐ መንገድ ይህን ይመስላል፡፡ ልብህ ታጥቦና ነጽቶ ሰላም ደስታና መተማመን ይሆንልሀል፡፡

በመጨረሻም ንስሐ በክርስቶስንና በእግዚአብሔርን ፍቃድ ደስ እየተሰኘህ አመስጋኝና ታማኝ እንድትሆን ያደርግሀል፡፡ ሞት ተፈርዶብንና መውጫው ጠፍቶን ሳለ ክርስቶስ “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ” (ማቴዎስ 11፥28) አለን። “እርሱ አስቀድሞ ወዶናልና እኛ እንወደዋለን” (1ዮሐንስ 4፥19)፡፡   

ለተጨማሪ መረጃ ያግኙን

በረሪ የውንጌል ጽሑፎችን (ትራክቶችን) ለማዘዝ

ልናቀው የሚገባ ከሁሉ የበለጠ ታሪክ

Bible and Candle

በመጀመሪያ አለማችን ባዶ ነበረች፡፡

አሶች በባህር፣

ከዋክብት በሰማይ ላይ አልነበሩም፤

የተሟላ መልዕክት ክፍል ልናቀው የሚገባ ከሁሉ የበለጠ ታሪክ

ባህርና ውብ አበቦች የሉም ነበር፡፡

ነገር ግን እግዚአብሔር ነበር፡፡

እግዚአብሔር አስደናቂ እቅድ ነበረው፡፡ ውብ የሆነች አለምን ለመስራት አሰበ፡፡ እንዳሰበም ፈጠራት፡፡ እግዚአብሔር አለምን ሲፈጥር ከምንም ነው የሰራት፡፡ “…..ይሁን” አለ፤ ሆነም!

ብርሀንን ፈጠረ፡፡ ወንዞችንና ባህርን፣ በሳር የተሸፈነች ምድርን፣ እንስሳትን፣ አእዋፋትንና ዛፎችን ሁሉ ሰራ፡፡

በመጨረሻ ሰውን ፈጠረ፡፡ ለፈጠረው ሰውም ሚስትን አበጀለት፡፡ ስማቸውም አዳምና ሔዋን ይባል ነበር፡፡

እግዚአብሐር አዳምና ሔዋንን በጣም ይወዳቸው ነበር፡፡ ይኖሩበት በነበረበት በውቡ ገነት ሁልግዜ አመሻሹ ላይ እየመጣ ያነጋግራቸው ነበር፡፡

አዳምና ሔዋን እግዚአብሔር ከከለከላቸው ከአንድ ዛፍ በስተቀር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዲበሉ ተፈቅዶላቸው ነበር፡፡

አዳምና ሔዋን የእግዚአብሔር ጠላት የሆነው ሰይጣን እስከፈተናቸው ቀን ድረስ በደስታ በገነት ይኖሩ ነበር፡፡ ነገር ግን አንድ ቀን እግዚአብሔር እንዳይበሉ ከከለከላቸው ዛፍ ፍሬ ለመብላት ወሰኑ፡፡ በዚህም ኃጢአትን ሰሩ፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ሀፍረትና ሀዘን ገባቸው፡፡

ከዚያን ጊዜ በኋላ ከእግዚአብሔር ጋር እንደ ቀድሞው መነጋገር አልቻሉም፡፡ ያንን ፍሬ ከበሉ በኋላ መከራና ችግር ሊደርስባቸውና ሞትን ሊሞቱ ሆነ፡፡ በሰሩት ስህተት እንዴት ያለ ሀዘንን አዝነው ይሆን!

እግዚአብሔር ሊረዳቸው ቃል ገባላቸው፡፡ የተወሰነው ጊዜ ሲደርስ ልጁን ኢየሱስን ወደ አለም እንደሚልክና ኢየሱስም ከሰማይ ወርዶ ኃጢአት ይቅር እንዲባል መንገድን እንደሚያበጅ ነበር ተስፋን የሰጠው፡፡ የኃጢአት ይቅርታ እንዲሆን ኢየሱስ ለሰው ሁሉ መከራን መቀበልና መሞት ነበረበት፡፡ አዳምና ሔዋን እግዚአብሔር አዳኝን እንደሚልክላቸው ሲያውቁ እንዴት ያለ ታላቅ ደስታ ተሰምቷቸው ይሆን!

አዳምና ሔዋን ልጆችንና የልጅ ልጆችን ወለዱ፡፡ ቀስ በቀስም ብዙ ሰዎች በዚች ምድር ላይ መኖር ጀመሩ፡፡

እግዚአብሔር ሁሉ ሰው ደስተኛ እንዲሆን ይፈልግ ነበር፡፡ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ነገራቸው፡፡ እግዚአብሔር እንዲያደርጉት የሰጣቸው ህግጋት ዝርዝር የሚከተለው ነው፡-

  1. ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ፡፡
  2. የተቀረጸውንም ምስል ለአንተ አታድርግ፡፡
  3. የእግዚአብሔርን የአምላክህን ስም በከንቱ አትጥራ፡፡
  4. የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ፡፡
  5. አባትህንና እናትህን አክብር፡፡
  6. አትግደል፡፡
  7. አታመንዝር፡፡
  8. አትስረቅ፡፡
  9. በባልንጀራህ ላይ በሐሰት አትመስክር፡፡
  10. የባልንጀራህን ቤት አትመኝ የባልንጀራህን ሚስት ሎሌውንም ገረዱንም በሬውንም አህያውንም ከባልንጀራህ ገንዘብ ሁሉ ማናቸውንም አትመኝ፡፡ (ዘጸአት 20፥3-17)

እነዚህን ህግጋት እኛም ማንበብ እንድንችል በመጽሐፍ ቅዱስ ተጽፈውልናል፡፡ ከታዘዝናቸውና ካደረግናቸው ደስተኞች እንሆናለን፡፡

ሰይጣን እነዚህን ህግጋት እንድንታዘዝ አይፈልግም፡፡ አንዳንዴ፣ በተለይም ደግሞ ሰው በማያየን ቦታ እንድንሰርቅ ይነግረናል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ሁሉን የሚያይ አምላክ ስለሆነ የምናደረገውን ሁሉ ያውቃል፡፡

ሰይጣን አንዳንድ ግዜ ውሸትን እንድንዋሽና የዋሸነውን ውሸት ማንም እንደማያውቅብን እንድናስብ ያደርገናል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ሁሉን የሚሰማ አምላክ ስለሆነ የምንለውን ሁሉ ያውቃል፡፡

አንዲህ ያሉ ኃጢአት ስንሰራ ውስጣችንን ሰላም አይሰማንም፡፡ እግዚአብሔር ስለሚወደን መልካም ሰዎች እንድንሆን ሊረዳን ይፈልጋል፡፡ ኢየሱስን ወደ አለም የላከውም ለዚህ ነው፡፡ የገባውን ተስፋ ፈጽሞ አልረሳም፡፡

ከብዙ አመታት በኋላ ኢየሱስ እንደ ሕጻን ተወለደ፡፡ አድጎም ሙሉ ሰው ሆነ፡፡

ብዙ አስደናቂ ነገሮችን አደረገ፡፡ ሕሙማን ፈወሰ፣ እውራንን አበራ፣ ሕጻናትን ባረከ፡፡

ኢየሱስ ምንም በደል አልሰራም ነበር፡፡ ይልቁንም ለሰዎች ስለ እግዚአብሔርና እንዴት ሊታዘዙት እንደሚገባ አስተማራቸው፡፡

ከጥቂት ጊዜ በኋላ የኢየሱስ ጠላቶች ኢየሱስን በመስቀል ሰቅለው ገደሉት፡፡

ኢየሱስ መከራን ተቀብሎ የሞተው ለሰው ልጆች ሁሉ ኃጢአት ሲሆን፤ ይህ መስዋዕቱ የሰቀሉትንም ሰዎች ኃጢአት ያካትት ነበር፡፡

ኢየሱስ ከሞቱ በኋላ ተቀበረ፡፡ ነገር ግን ከዛን በኋላ አስደናቂ ነገር ሆነ፡፡ ኢየሱስ እንደተቀበረ አልቀረም፤ ከሙታን ተነሳ፡፡

ከትንሳኤው ጥቂት ጊዜ በኋላ እግዚአብሔር ኢየሱስን በደመና ወደ ሰማይ ወሰደው፡፡ መላዕክት ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲያርግ ቆመው ሲመለከቱ ለነበሩ ደቀ መዛሙርቱ ተመልሶ እንደሚመጣ ነገሯቸው፡፡

ኢየሱስ የሞተው ለእኛም ኃጢአት ጭምር ነው፡፡ ኃጢአታችንን ተጸጽተን እንድንናዘዝና ንስሀ እንድነገባ ይፈልጋል፡፡ ይህንን ብናደርግ ይቅርታን ሊሰጠን ዝግጁ ነው፡፡

በማንኛውም ግዜ ወደ እግዚአብሔር መጸለይ ትችላለህ፡፡ እርሱ እያንዳንዷን ቃላችንን የሚሰማና ሀሳባችንን ሁሉ የሚያውቅ አምላክ ነው፡፡ ኃጢአታችን ይቅር ሲባልልን በውስጣችን ደስታ እንዲሰማን ያደርጋል፡፡ ከዛም መልካም የሆነውን ሁሉ ለማድግ የምንፈልግ ሰዎች እንሆናለን፡፡

እግዚአብሔርን አለመታዘዝና ሰይጣንን መከተል እንመርጥ ይሆናል፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔር ቃል በዚህ ዓለም በምኖርበት ጊዜ ለእግዚአብሔር ጥሪ ምላሻችን እምቢታ ከሆነ ወደ ገሀነም እንደምንጣል ይነግረናል፡፡ ገሀነም ለዘላለም ሲነድ የሚኖር እሳት ነው፡፡

ነገር ግን ኢየሱስን ብንወደውና ብንታዘዘው ወደ ምድር መጥቶ በሚመለስበት ጊዜ ወደ ሰማይ ይዞን ይሄዳል፡፡ መንግስተ ሰማይ የእግዚአብሔርና የልጁ የኢየሱስ ውብ መኖሪያ ነው፡፡ የፍቅርና የብርሀን ቤት ነው፡፡ በእዚያ ለዘላለም በደስታ እንኖራለን፡፡

ለተጨማሪ መረጃ ያግኙን

በረሪ የውንጌል ጽሑፎችን (ትራክቶችን) ለማዘዝ

ከሞት በኋላስ?

በአሁኑ ወቅት ሕያው ነዎት፤ ይተነፍሳሉ፤ ከቦታ ቦታ ይንቀሳቀሳሉ፤ ስራዎንም ያከናውናሉ፡፡ እየኖሩ ያሉት ሕይወት በምቾት ወይም በችግር የተሞላ ሕይወት ይሆናል፡፡ ፀሀይ ትወጣለች ደግሞም ትጠልቃለች፤ በአንድ ስፍራ ህጻን ይወለዳል በሌላ ስፍራ ደግሞ አንዱ ይሞታል፡፡

ሕይወት በአጠቃላይ ጊዜያዊ ቅንብር ነች፡፡

ነገር ግን

እርስዎ ከሞቱ በኋላ ወዴት ይሄዳሉ?

ኃይማኖተኛ ሰው ቢሆኑ፤ ወይም

ምንም አይነት ኃይማኖት ባይኖርዎ

ይህንን መሰረታዊ ጥያቄ መመለስ

ይኖርብዎታል፡፡ ምክንያቱም ሰው

ሁሉ ከአጭር የምድራዊ ቆይታው

በኋላ ወደ ዘላለም መኖሪያው

ያመራልና (መክብብ 12፡5)፡፡

ግን ወዴት?

የሚቀበሩበት የመቃብር ስፍራ ነፍሶን ማስቀረት አይቻለውም፡፡ በድንዎ በእሳት ተቃጥሎ ቢጠፋ፤ ነፍስዎን እሳት አይበላትም፡፡ በጥልቁ ባህር ውስት ገብተው ቢጠፉ፤ ነፍስዎ አትሰምጥም፡፡

ነፍስዎ በፍጹም አትሞትም!

የሰማይ እና የምድር ሁሉ አምላክ

የተሟላ መልዕክት ክፍል ከሞት በኋላስ?

“ነፍስ ሁሉ የኔ ናት” ብሎአል፡፡

ከዚህ ሕይወት በኋላ እውነተኛ ማንነትዎ የሆነችው ነፍስዎ፤ በሕይወት በምድር ላይ በነበሩበት ወቅት ከሰሯቸው መልካምም ይሁን ክፉ ስራዎት ጋር ትገናኛለች፡፡ ዕብራውያን 9፡27ን መልከቱ፡፡

ከልብዎ የሚያመልኩ ሰው ይሆኑ ይሆናል

ስለሚሰርዋቸው ያለተገቡ ተግባራት ይጸጸቱ ይሆናል

የሰረቁትን መልሰው ይሆናል

እነዚህ ሁሉ የሚያስፈልጉ ነገሮች ቢሆኑም

ስለ ኃጢአትዎ በራስዎ ስርየትን ማምጣት አይችሉም

በምድር ሁሉ ላይ ፈራጅ የሆነው የሰማይ አምላክ እግዚአብሔር ከፊቱ የተሰወረ አንዳች ነገር ስለሌለ የእርስዎን ኃጢአት እና ሕይወት በአጠቃላይ ያውቃል፡፡ እርስዎ ከነኃጢአትዎ ከሆኑ ሊመጣ ካለው ከእግዚአብሔር ክብርና ባርኮት ሊካፈሉ አይችሉም፡፡

ነገር ግን የኸው የሰማይ አምላክ የፍቅር አምላክ ነው፡፡ ለሕወትዎና ለነብስዎ የመዳኛ መንገድ ስላዘጋጀ የዘላለም ጥፋት ወደ ሆነው ወደ ገሃነም እሳት መጣል የለብዎትም፡፡ እግዚአብሔር ኢየሱስን ወደዚህ ምድር የላከው የእርስዎን ነብስ ለማዳን ነው፡፡ ኢየሱስ በቀላንዮ መስቀል ላይ ተሰቃይቶ ሲሞት የእርስዎ ኃጢአት ሁሉ በእርሱ ላይ ሆንዋል፡፡ እግዚአብሔር ሰማይ ሊያቀርብ የሚችለውን ድንቁን መስዋዕት ስለ እርስዎ ኃጢአት ሲል ሰጥትዋል፡፡ “እርሱ ግን ስለ መተላለፋችን ቈሰለ፥ ስለ በደላችንም ደቀቀ የደኅንነታችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቍስል እኛ ተፈወስን” (ኢሳይያስ 53፥5)፡፡ እነዚህ የትንቢት ቃላት የተነገሩት ኢየሱስ ወደ ምድር ከመምጣቱ ከብዙ ዘመናት በፊት ነው፡፡

ኢየሱስ እንደሚወድዎ ያምናሉ? ወደ እርሱ በመጸለይ ኃጢአትዎን ይናዘዛሉ? ንስሀ በመግባት የእግዚአብሔር ልጅ በሆነው በኢየሱስ ያምናሉ? በፍጹም መሰጠት ወደ እርሱ ከመጡ ለነብስዎ ሰላምን እንዲሁም ከሞት በኋላ የከበረ ሕይወትን ይሰጥዎታል፡፡ በሀሴት የተሞላ የዘላለም ቤትና የነብስ ሰላም እንዳልዎት እርግጠኛ መሆን የሚችሉት ይህንን ወሳኔ ሲወስኑ ብቻ ነው፡፡

ግን’ኮ አዳኝ የሆነውን የኢየሱስን ፍቅር በሕይወት ዘመናቸው ላልተቀበሉ ሁሉ የጥፋት ጉድጓድና ማብቂያ የሌለው የዘልለም እሳት ይጠብቃቸዋል፡፡ ከሞት በኋላ ወደ ኋላ መመለስና የመዳን ተስፋ ሁሉ ያበቃለታል፡፡

“በዚያን ጊዜ በግራው ያሉትን ደግሞ ይላቸዋል። እናንተ ርጉማን፥ ለሰይጣንና ለመላእክቱ ወደ ተዘጋጀ ወደ ዘላለም እሳት ከእኔ ሂዱ” (ማቴ. 25፥41)፡፡ “የማይጠቅመውንም ባሪያ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት፤ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል” (ማቴ. 25፥30)፡፡  

እግዚአብሔር፤ በመጽሐፍ ቅዱስ፤ በምድር ሁሉ ላይ ሊመጣ ስላለው የመጨረሻ ፍርድ አስጠንቅቋል፡፡ በእነዚህ ቅዱሳት መጻሕፍት ይህ የፍርድ ቀን ከመምጠቱ በፊት ግልጽና ተጨባጭ ምልክቶች እንደሚሆኑ ተጽፍዋል፡፡

ከመምጣቱ በፊት ጦርነትና የጦርነት ወሬ በየቦታው ይሰማል፤ ሕዝብ በሕዝብ ላይ ተነስቶ እርስ በእርስ አለመግባባት እና መፋጀት ይሆናል፤ መንግስታትም በመካከላቸው የሚነሳውን የሀሳብ ልዩነት እና አለመግባባት መፍታት ያቅታቸዋል፡፡

በተለያዩ ስፍራዎች የምድርም መናወጥና ቸነፈር ይሆናል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በዚህ ወቅት ክፉዎች በክፋታቸው እየባሱ እንደሚሄዱ ይነግረናል፡፡ ብዙዎችም የእግዚአብሔርን ማስጠንቀቂያ ቸል በማለት ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፡፡ በዘመናችን እነዚህን ትንቢቶቸ ሲፈጸሙ እያየን አይደለምን? ማቴዎስ 24፥6-7፤12 እና 2ኛ ጢሞቴዎስ 3፥4ን ይመልከቱ፡፡

አንድ ቀን ሁላችንም ለፈጸምናቸው ድርጊቶች ሁሉ ልንዳኝ ከፈጣሪያችን እና ጌታችን ፍርድ ወንበር ፊት እንቆማለን (ማቴዎስ 25፥32-33)፡፡ ጻድቅና ታላቅ ፈራጅ የሆነው አምላካችን በብልጽግናችን በድህነታችን፤ በእውቅናችን በመዋረዳች፤ በቆዳችን ቀለም፤ በዘራችን ላይ ያለተመሰረተ ጻድቅ ፍርድ እነደሚያስተላልፍ መዘንጋት የለብንም፡፡ 

ማብቂያ በሌለው ዘላለም ውስጥ የሰዓት መቁጠሪያና ዓመታዊ ቀን መቁጠሪያ (ካላንደር) አይኖሩም፤ ዘመናቱም መጨረሻቸው አይታወቅም፡፡ የኃጢአተኞችና እግዚአብሔርን ያልፈሩቱ የስቃያቸው ጭስ ለዘላለም በገሀነም ሲጬስ፤ የዳኑቱ ደስታ ዝማሬ በረከትና መጽናናት ማብቂያ በሌለው በእግዚአብሔር መንግስት ውስጥ ያስተጋባል፡፡ ምርጫዎን አሁኑኑ ይወስኑ፤ ምክንያቱም ይህ እድል በቅጽበት ከእጅዎ ሊወጣ ይችላልና፡፡ “እነሆ፥ የተወደደው ሰዓት አሁን ነው፤ እነሆ፥ የመዳን ቀን አሁን ነው” (2ቆሮንጦስ 6፥2) ፤ ማቴዎስ 11፥28፡፡

ለተጨማሪ መረጃ ያግኙን

በረሪ የውንጌል ጽሑፎችን (ትራክቶችን) ለማዘዝ